| 14፥6 | የእግዚአብሔርም መንፈስ በእርሱ ላይ በኃይል ወረደ ጠቦትን እንደሚቆራርጥ በእጁ ምንም ሳይኖር ቈራረጠው ያደረገውንም ለአባቱና ለእናቱ አልነገረም። |
| 14፥7 | ወርዶም ከሴቲቱ ጋር ተነጋገረ እጅግም ደስ አሰኘችው። |
| 14፥8 | ከጥቂትም ቀን በኋላ ሊያገባት ተመለሰ፥ የአንበሳውንም ሬሳ ያይ ዘንድ ከመንገድ ፈቀቅ አለ እነሆም፥ በአንበሳው ሬሳ ውስጥ ንብ ሰፍሮበት ነበር፥ ማርም ነበረበት። |
| 14፥9 | በእጁም ወስዶ መንገድ ለመንገድ እየበላ ሄደ ወደ አባቱና ወደ እናቱ መጣ፥ ማሩንም ሰጣቸው፥ እነርሱም በሉ ማሩንም ከአንበሳው ሬሳ ውስጥ እንደ ወሰደ አልነገራቸውም። |
| 14፥10 | አባቱም ወደ ሴቲቱ ወረደ ጎበዞችም እንዲህ ያደርጉ ነበርና ሶምሶን በዚያ በዓል አደረገ። |
| 14፥11 | ባዩትም ጊዜ ከእርሱ ጋር ይሆኑ ዘንድ ሌሎች ሠላሳ ሰዎች ሰጡት። |
| 14፥12 | ሶምሶንም። እንቆቅልሽ ልስጣችሁ በሰባቱም በበዓሉ ቀኖች ውስጥ ፈትታችሁ ብትነግሩኝ፥ ሠላሳ የበፍታ ቀሚስና ሠላሳ ልውጥ ልብስ እሰጣችኋለሁ |
| 14፥13 | መፍታትም ባትችሉ ሠላሳ የበፍታ ቀሚስና ሠላሳ ልውጥ ልብስ ትሰጡኛላችሁ አላቸው። እርሱም፦ እንድንሰማው እንቆቅልሽህን ንገረን አሉት። |
| 14፥14 | እርሱም፦ ከበላተኛው ውስጥ መብል ወጣ፥ ከብርቱም ውስጥ ጥፍጥ ወጣ አላቸው። ሦስት ቀንም እንቈቅልሹን መተርጎም አልቻሉም። |
| 14፥15 | በአራተኛውም ቀን የሶምሶንን ሚስት። እንቈቅልሹን እንዲነግረን ባልሽን ሸንግዪው፥ አለዚያም እንቺንና የአባትሽን ቤት በእሳት እናቃጥላለን ወደዚህ ጠራችሁን ልትገፉን ነውን? አሉአት። |
| 14፥16 | የሶምሶንም ሚስት በፊቱ እያለቀሰች። በእውነት ጠልተኸኛል፥ ከቶም አትወድደኝም ለሕዝቤ ልጆች እንቈቅልሽ ሰጥተሃቸዋልና ትርጓሜውንም አልነገርኸኝም አለችው። እርሱም፦ እነሆ፥ ለአባቴና ለእናቴ አልነገርኋቸውም፥ ለአንቺ እነግርሻለሁን? አላት። |
| 14፥17 | ሰባቱንም የበዓል ቀን በፊቱ አለቀሰች እርስዋም ነዝንዛዋለችና በሰባተኛው ቀን ነገራት። ትርጓሜውንም ለሕዝብዋ ልጆች ነገረች። |
| 14፥18 | በሰባተኛውም ቀን ፀሐይ ሳትገባ የከተማይቱ ሰዎች። ከማር የሚጣፍጥ ምንድር ነው? ከአንበሳስ የሚበረታ ማን ነው? አሉት። እርሱም፦ በጥጃዬ ባላረሳችሁ የእንቈቅልሼን ትርጓሜ ባላወቃችሁ ነበር አላቸው። |
| 14፥19 | የእግዚአብሔርም መንፈስ በላዩ በኃይል ወረደ ወደ አስቀሎናም ወረደ፥ ከዚያም ሠላሳ ሰዎችን ገደለ፥ ልብሳቸውንም ወስዶ እንቈቅልሹን ለፈቱት ሰዎች ሰጠ። ቍጣውም ነደደ፥ ወደ አባቱም ቤት ወጣ። |
| 14፥20 | የሶምሶን ሚስት ግን ከተባበሩት ከሚዜዎቹ ለአንደኛው ሆነች። |