| 14፥1 | ከሴት የተወለደ ሰው
የሕይወቱ ዘመን ጥቂት ቀን ነው፥ መከራም ይሞላዋል። |
| 14፥2 | እንደ አበባ ይወጣል፥ ይረግፋልም
እንደ ጥላም ይሸሻል፥ እርሱም አይጸናም። |
| 14፥3 | እንደዚህስ ባለ ሰው ላይ ዓይኖችህን ትከፍታለህን?
ከአንተስ ጋር እኔን ወደ ፍርድ ታገባለህን? |
| 14፥4 | ከርኩስ ነገር ንጹሕን ሊያወጣ ማን ይችላል?
አንድ እንኳ የሚችል የለም። |
| 14፥5 | የሰው ዕድሜ የተወሰነ ነው፥
የወሩም ቍጥር በአንተ ዘንድ ነው፥
እርሱም ሊተላለፈው የማይችለውን ዳርቻ አደረግህለት። |
| 14፥6 | እንደ ምንደኛ ዕድሜው እስኪፈጸም ድረስ
ያርፍ ዘንድ ከእርሱ ጥቂት ዘወር በል። |
| 14፥7 | ዛፍ ቢቈረጥ ደግሞ ያቈጠቍጥ ዘንድ፥
ቅርንጫፉም እንዳያልቅ ተስፋ አለው። |
| 14፥8 | ሥሩም በምድር ውስጥ ቢያረጅ፥
ግንዱም በመሬት ውስጥ ቢሞት፥ |
| 14፥9 | ከውኃ ሽታ የተነሣ ያቈጠቍጣል
እንደ አትክልት ቅርንጫፍ ያወጣል። |
| 14፥10 | ሰው ግን ይሞትና ይጋደማል
ሰውም ነፍሱን ይሰጣል፥ እርሱስ ወዴት አለ? |
| 14፥11 | ውኃ ከባሕር ውስጥ ያልቃል
ወንዙም ያንሳል ይደርቅማል። |
| 14፥12 | ሰውም ተኝቶ አይነሣም
ሰማይ እስኪያልፍ ድረስ አይነቃም፥
ከእንቅልፉም አይነሣም። |
| 14፥13 | በሲኦል ውስጥ ምነው በሰወርኸኝ ኖሮ!
ቍጣህ እስኪያልፍ ድረስ በሸሸግኸኝ ኖሮ!
ቀጠሮም አድርገህ ምነው ባሰብኸኝ ኖሮ! |
| 14፥14 | በውኑ ሰው ከሞተ ተመልሶ ሕያው ይሆናልን?
መለወጤ እስኪመጣ ድረስ፥
የሰልፌን ዘመን ሁሉ በትዕግሥት በተጠባበቅሁ ነበር። |
| 14፥15 | በጠራኸኝና በመለስሁልህ ነበር
የእጅህንም ሥራ በተመኘኸው ነበር። |