| መጽሐፈ ምሳሌ 22 |
| 1 | መልካም ስም ከብዙ ባለጠግነት ይሻላል፥ መልካምም ሞገስ ከብርና ከወርቅ ይበልጣል። |
| 2 | ባለጠጋና ድሀ ተገናኙ እግዚአብሔር የሁላቸው ፈጣሪ ነው። |
| 3 | ብልህ ሰው ክፉን አይቶ ይሸሸጋል አላዋቂዎች ግን አልፈው ይጐዳሉ። |
| 4 | ትሕትናና እግዚአብሔርን መፍራት ባለጠግነት ክብር ሕይወትም ነው። |
| 5 | እሾህና ወጥመድ በጠማማ ሰው መንገድ ናቸው ነፍሱን ግን የሚጠብቅ ከእነርሱ ይርቃል። |
| 6 | ልጅን በሚሄድበት መንገድ ምራው፥ በሸመገለም ጊዜ ከእርሱ ፈቀቅ አይልም። |
| 7 | ባለጠጋ ድሆችን ይገዛል፥ ተበዳሪም የአበዳሪ ባሪያ ነው። |
| 8 | ኃጢአትን የሚዘራ መከራን ያጭዳል፥ የቍጣውም በትር ይጠፋል። |
| 9 | ርኅሩህ የተባረከ ይሆናል፥ ከእንጀራው ለድሀ ሰጥቶአልና። |
| 10 | ፌዘኛን ብታወጣ ክርክር ይወጣል፥ ጠብና ስድብም ያልቃል። |
| 11 | የልብን ንጽሕና የሚወድድና ሞገስ በከንፈሩ ያለች፥ ንጉሥ ወዳጁ ይሆናል። |
| 12 | የእግዚአብሔር ዓይኖች እውቀትን ይጠብቃሉ እርሱ ግን የወስላታውን ቃል ይገለብጣል። |
| 13 | ታካች ሰው። አንበሳ በሜዳ ነው በመንገዱ ላይ እሞታለሁ ይላል። |
| 14 | የጋለሞታ ሴት አፍ የጠለቀ ጕድጓድ ነው እግዚአብሔር የተቈጣው በእርስዋ ይወድቃል። |
| 15 | ስንፍና በሕፃን ልብ ታስሮአል የተግሣጽ በትር ግን ከእርሱ ያርቃታል። |