ሰላም
ይሁዳን እና አይሁዳውያንን ለያይተንም ማየት ያለብን ይመስለኛል። ይሁዳ አንድ ግለሰብ ነው፤ አይሁዳውያን ደግሞ እስራኤላውያን ናቸው። በመሰረቱ ሰው መጥፎ ሲሆን "ይሄ ይሁዳ ነው" ነው እንጂ የሚባለው "አይሁዳዊ ነው" አይባልም። ይህ ብቻ አይደለም ኢየሱስም ራሱ አይሁዳዊ ወይም እስራኤላዊ ነበረ። ከዚህም በተጨማሪ 12ቱ ሃዋርያት እንዲሁም ጳውሎስ ሁሉ አይሁዳውያን ነበሩ። ስለዚህ አይሁዳውያንን መጥላት የሚባል ነገር ፈጽሞ መጽሃፍ ቅዱሳዊ አይደለም።
በእርግጥ የአስቆሮቶ ይሁዳ ኢየሱስን ለገንዘብ ሲል አሳልፎት እንደሰጠ በአዲስ ኪዳን ተጽፎአል። የአይሁዳውያን መሪዎችም እንዲሁ ኢየሱስን በሞት እንዲቀጣ ለጲላጦስ አሳልፈው ሰጥተውታል። አንደኛ የአይሁድ ህዝብ ሁሉ አይደለም ኢየሱስን አሳልፎ የሰጠው፤ በተለይ ደግሞ የካህናት አለቆች ናቸው። የተወሰኑ አይሁዳውያን ደግሞ ኢየሱስን እንደ ነብይ ያዩና ይከተለቱም ነበር። ስለዚህ ሁሉንም አይሁዳውያን በአንድ ላይ መጨፍለቅ ከእውነት የራቀ ነው።
ይህ ሁሉ ደግሞ አንተ እንዳልከው አስቀድሞ እግዚአብሔር በነብያቱ የተናገረው ነገር ስለሆነ ይሁዳንም ይሁን የአይሁድ መሪዎችን ከእኛ የተለዩ ልዩ ሰይጣኖች አድርገን መመልከት የለብንም። ኢየሱስ በእኛ በሁላችን ኃጢአት ምክንያት ሞተ እንጂ በእነርሱ ኃጢአት ብቻ አልሞተምና። በኢየሱስ ሞት እኛ ሁላችን ተካፋዮች ነንና።
በተለይ ደግሞ አይሁዶችን ማለትም እስራኤላውያንን እንዳንጠላና በእነርሱ ላይ የትዕቢትን ነገር እንዳንናገርና እንዳንመጻደቅ ጳውሎስ በሮሜ መልእክቱ ያስጠነቅቀናል (ሮሜ ምእራፍ 9 እስከ ምእራፍ 11)። ምንም እንኳን ለጊዜው የክርስቶስ ነገር ቢሸፈንባቸውም አሁንም እግዚአብሔር አልጣላቸውም፤ የገባላቸውንም ተስፋ አልተወውም።
Quote:
ወደ ሮሜ ሰዎች 11
18 ብትመካባቸው ግን ሥሩ አንተን ይሸከምሃል እንጂ ሥሩን የምትሸከም አንተ አይደለህም።
19 እንግዲህ፦ እኔ እንድገባ ቅርንጫፎች ተሰበሩ ትል ይሆናል።
20 መልካም፤ እነርሱ ከአለማመን የተነሣ ተሰበሩ አንተም ከእምነት የተነሣ ቆመሃል። ፍራ እንጂ የትዕቢትን ነገር አታስብ።
21 እግዚአብሔር እንደ ተፈጠሩት ለነበሩት ቅርንጫፎች የራራላቸው ካልሆነ ለአንተ ደግሞ አይራራልህምና።